Saturday, October 20, 2012

ስልጣንን ከኦርቶዶክስ እና ከአማራ ነጥቅናት !!! “የስብሃት ነጋ ቅኔ”


ህወሃት ጠላቶቼ ናቸው ብሎ ከሚቆጥራቸው መካከል ዋነኞቹ የአማራ ህዝብና፤ የኦሮቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን
ናቸው። እዚህ ላይ “ተፈጥሮና አማራ የትግራይ ህዝብ ቀንደኛ ጠላቶች ናቸው”  ብለው ጽፈው የተማማሩበትን
ማስታወስ ያስፈልጋል። ኦሮቶዶክስ ቤተክርስትያን እያለችም እቅዳችንን ማስፈጸም አንችልም ባሉት መሠረትም
ቤተክርስትያኒቷን ለሦስት እንድትከፈል ማድረጋቸውም የሚዘነጋ አይደለም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከቂምና በቀል በስተቀር ፍቅርን የማያውቀው እና በእርጅና ዘመኑ እንኳ ራሱን መግራት ያቃተው
ስብሃት ነጋ የተባለው ክፉ ዘረኛ በቅርቡ “ስልጣንን ከኦሮቶዶክስና ከአማራ እጅ ነጠቅናት ይህም የትግላችን ውጤት ነው” 
ማለቱን ሰምተናል። ባለፉት አርባ ዓመታት የትኛው አማራ፤ የትኛው ኦሮቶዶክስ ስልጣን ይዞ ነበር ቢባል ግን መልስ
የለውም። የከሃዲው ስብሃት ነጋ አባባል ግን ለአማራ ህዝብና ለኦሮቶዶክስ ቤተክርስትያን ያለውን ሥር የሰደደ ጥላቻ
ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው። መለስ ዜናዊም በህይወት ዘመኑ ለቤተክርስትያኒቷና ለአማራ ህዝብ ባለው ጥላቻ
መሠረት ቤተክርስትያኒቷን ለማፍረስ የቻለውን ሁሉ አድርጓል። የአማራንም ህዝብ ለማጥፋት ብዙ አረመኔያዊ
ተግባራትን ፈጽሟል።በእርሱ የአገዛዝ ዘመን ከሁለት ሚሊዮን በላይ አማራ ከቁጥሩ ጎድሎ የት እንደገባ ሳይታወቅ
ቀርቷል።
ከሁለት ሚሊዮን በላይ የአማራ ህዝብ የት ገባ ተብሎ የተጠየቀው መለስ ዜናዊ ያለምንም እፈረትና ታሪክና ሰው ምን
ይለኛል ሳይል “በኤድስ አልቋል” ብሎ በድፍረት መልስ ሰጥቷል።ይሄ በጣም አሳፋሪ እና ነውር ነገር ነው። በተለይም
አገርን እመራለሁ ብሎ በህዝብ አናት ላይ ከተቀመጠ ሰው አንደበት ሲወጣ። ህወሃቶች እንዲህ ያለውን አሳፋሪንና ነውር
ነገረን ለይተው አያውቁም ማለት አይቻልም። አንድን ህዝብ ለይተው “በኤድስ አለቀ” ብሎ መናገር ነውር መሆኑን
ጠንቅቀው ያውቃሉ። ነውር መሆኑን እያወቁ እንዲህ ያለ አሳፋሪ ነገር በአደባባይ እንዲናገሩ የሚያደርጋቸው በእድሜም
ሆነ በትምህርት መገራት ያልቸለው ትእቢታቸውና በአጠቃላይ ለአማራ ህዝብ ያላቸው ሥር የሰደደ ጥላቻ መሆኑን
መገንዘብ ያስፈልጋል። ህወሃት ራሱን የአማራ ህዝብ ጠላት ነኝ ብሏል። ህወሃትን ጠላት አይደለም ብሎ መከራከር
እማይቻልበት ደረጃ ላይም ተደርሷል።በጋምቤላ እና በኦጋዴን ላይ የተፈፀመው ግድያ በዘር ማጥፋት ወንጀል ውስጥ
ተመድቧል። በኦሮሞ እና በደቡብ ህዝቦች ላይ የተፈፀመውን ወንጀል ዘርዝረነው አንዘልቅም። የህወሃት ህልም
በማንኛውም መንገድ ስልጣኑን ይዞ እርሱና እርሱ የፈቀደላቸው ብቻ ሲኖሩ ሌላው የእነርሱ አኗኗሪ ሁኖ እንዲኖር ነው።
ህልምና ራዕያቸውም እነርሱ የበላይ ሌላው የበታች ተኩኖ የሚኖርበት ሥርዓት እንዲገነባ ነው።እንዲህ ያለ ነገር
አይጠቅምም የሚለውን ሁሉ አሸባሪ እና ጠላት ነው ብለው የቻሉትን ገድለዋል፤ ለመግደል ያልቻሉትንም የእድሜ ልክ
እስራት ፈርደዋል።ይሄ ሁሉ ተደምሮ የሚያሳየን ህወሃቶች የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላቶች መሆናቸውን ነው እንጂ ወዳጆች
መሆናቸውን አይደለም። እንግዲህ ትግሉም መቀኘት ያለበት ከዚህ አቅጣጫ መሆን ይኖርበታል።
እናንተ እየመራችሁኝ እኔ እየተከተልኳችሁ እንዘልቃለን ያለው ኃ/ማሪያም ደሳለኝ የተባለው ግለሰብ በጠቅላይ
ሚንስትርነት ከተመደበ በኋላ የህወሃት አባት ነው የሚባለው ስብሃት ነጋ “ስልጣንን ከኦርቶዶክስና ከአማራ ነጠቅናት” 
ብሎ መናገሩ ለአማራው ህዝብ እና ለኦሮቶዶክስ ቤተክርስትያን ያለውን ጥላቻ ከማሳየት በቀር ያሳየው በጎ ነገር የለም።
ስብሃት ነጋም ሊነግረን የፈለገው መልእክት ለአማራና ለቤተክርስትያኒቷ ያለውን ጥላቻ እንጂ ፍቅርን አይደለም። ይሄ

ማለት ሌሎችን ህዝቦች ይወዳል ማለት አይደለም። አሁንም ደግመን እንናገራለን ይህ ግለሰብና ቡድኑ በአጠቃላይ
የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላቶች ናቸው።
ህወሃት እንደ ህዝብ አማራን፤ እንደ ድርጅት ኦሮቶዶክስ ኃይማኖትን ለማጥፋት የጭካኔ ሰይፉን ከሰገባው የመዘዘው ገና
ድሮ ሕፃን ሳለ መሆኑ ይታወቃል።ባለፉት ሃያ አንድ ዓመታት የአማራን ህዝብ ቀጥቅጠዋል፤ አዋርደዋል፤ ገድለዋል፤
አሳደዋል፤ ለርሃብና ለእርዛት ዳርገዋል። በአማራ ህዝብ ላይ የተነዛው የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ እና የተፈፀመው ወንጀል
መቼም መቼም የሚረሳ አይደለም። በተመሳሳይ ሁኔታ ኦሮቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያንን የዘረኞችና የአመንዝሮች
መጫወቻ አድርገዋታል። አሁን ደግሞ አንድነቱን ጠብቆ ለብዙ ዘመን የኖረውን የሙስሊሙን ማህበረሰብ ለመበጥበጥ
የጥፋት ሰይፋቸውን መዘዋል። በኦሮቶዶክስ ቤተክርስትያን ላይ አባ ገ/መድህንን በመሾም ቤተክርስትያኒቷን
እንዳዋረዷት ሁሉ በሙስሊምሙ ላይ ታማኝ ካድሬያቸውን በመሾም የምእመኑን አንድነት ለማፍረስ ሌተ ተቀን
እየማሰኑ ይገኛሉ። ይሄ ድንቁርና የወለደው ትዕቢት የሚተነፍስበት ግዜ ግን እሩቅ አይሆንም።
የተከበራችሁ ወገኖቻችን !
ህወሃቶች ከጥፋታቸው መመለስ የሚችሉ አይደሉም። የህዝቡን ትእግስት እንደፍርሃት ቆጥረው “ሽንታም”  ብለው
ከመሳደብ ተመልሰው ወደ ልቦናቸው የሚመጡ አይደሉም። ካለኛ ጀግና ካለኛ ሰው የለም ብለውም የእኛን እድል
ፈንታ ወሳኞች እነርሱ ሁነዋል። ኢትዮጵያዊያንም እነርሱ ሲፈቅዱ የሚኖሩ፤ እነርሱ ካልፈቀዱለትም መኖር የማይችሉ
ዜጎች ሁነዋል። እኛ ወርቅ አንተ ግን ወርቅ ያልሆንክ ብለው በአደባባይ መናገራቸውንም በትዝብት ተመለክተናል።
እንግዲህ እስከ መቼ በህወሃቶች ፈቃድ እንኖራለን ?አስከመቼስ እነርሱ ለይተው በወሰኑልን መንገድ
እንጓዛለን ?እንዴትስ የእነርሱ አኗኗሪ ሁነን እንዘልቃለን?
የተከበራችሁ ወገኖቻችን ሆይ !
አሁን ለራሱ ክብር የሚሰጥ ዜጋ ትክክለኛውን መልስ ይፈልግ።ትክክለኛዋ መልስ ከሂሊናችን ማህደር ውስጥ አለች።
እርሷም “ ነፃነት ወይም ሞት ! ” የምትል ነች።
ግንቦት ሰባት የፍትህ፤ የነጻነትና የዴሞክራስ ንቅናቄ ለጥያቄዋ መልስ አግኝተን ነፃነት ወይም ሞት ካልን ቆይተናል።
ህወሃቶች ተጭነውን እኛ ተሸክመናቸው አብረን ልንኖር አንችልም። እነርሱም ሳይጫኑን እኛም ሳንሸከማቸው በነፃነት
የምንኖርባት ኢትዮጵያ እስከምትፈጠር ድረስ የምር ከመታገል ውጪ ሌላ አማራጭ አለ ብለን አናምንም።ስለዚህ
የጀመርነውን ትግል በጀመርነው መንገድ አጠናክረን እንቀጥላለን። ህወሃቶች የተመረኮዙት የሸንበቆ ምርኩዝ ተሰብሮ
የነፃነት ጎህ እስኪቀድ ድረስ ሳናፈገፍግ እንታገላለን። እናሸንፋለንም።ያን ግዜም ስልጣንን ከዚህ ህዝብ ከዚያ ህዝብ
ነጠኳት የሚል ትዕቢተኛ አይኖርም።ስልጣን ከኢትዮጵያ ህዝብ የሚሰጥ እንጂ የሚነጠቅ አይደለም።